Dreba Cement Factory Is Going to Manufacture Cement Which Will Be Used For Simple Construction
የደርባ ሲሚንቶ ፋብሪካ ለቀላል ግንባታዎች የሚያገልግል ሲሚንቶ ሊያመርት ነው
የደርባ ሲሚንቶ ፋብሪካ ለቤትና ለቀላል የግንባታ ስራዎች የሚያገልግል የሲሚንቶ ዓይነት ሊያመርት ነው። ሲሚንቶው ከሶስት እስከ ስድስት ወራት ውስጥ ለገበያ ይቀርባል ብሏል ፋብሪካው።
በሚድሮክ ኢትዮጵያ የደርባ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ኃይሌ አሰግዴ እንደሚሉት ፥ እንደ ባቡር፣ የስኳርና የሪል ስቴት አይነቶቹ ግዙፍ ፕሮጀክቶች መጀመር ፥ አሁን ያለውን የሲሚንቶ ፍላጎት ከፍ ስለሚያደርጉት ለዚህ ፍላጎት መሟላት ደርባ የሚጠበቅበትን ሊወጣ ተዘጋጅቷል ።ፋብሪካው ከግዙፍ ፕሮጀክቶች ባሻገር አብዛኛውን ማህበረሰብ ባማከለ መልኩ ፥ አነስተኛ ጥንካሬ የሚፈልጉ ለተለያዩ ግንባታዎች የሚያገልግሉ የሲሚንቶ አይነቶችን ማምረት ዕቅድ አንዳለው ነው ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት የተናገሩት።እነዚህን ከፍተኛ ጥንካሬ ያለው ሲሚንቶ የማይፈልጉ ስራዎችን ለመስራት የሚያስችሉ የሲሚንቶ አይነቶችን ለማምረት ኩባንያው ሙሉ ዝግጅቱን አጠናቃል ብለዋል ።
ሲሚንቶው መዋል ያለበት ለየትኞቹ የግንባታ አይነቶች መሆኑን የመቆጣጠር ስራውን የሚሰራ አካል ያስፈልጋል ያሉት አቶ ሀይሌ ፥ ይህም በቀላል ዋጋ ስለተገኘ ብቻ ግንባታዎች መሰራት ባለባቸው ጥራትና አይነት ሳይሰሩ እንዳይቀሩ ለመከታተል ይረዳል ባይ ናቸው ።
በአሁኑ ወቅት ወደ ስራ የገቡ 20 የሲሚንቶ ፋብሪካዎች በሃገሪቱ የሚስተዋለውን የሲሚንቶ ፍላጎትና የአቅርቦት ፥ አለመመጣጠን እየቀረፉ ናቸው ።
ከአምስት ዓመት በፊት አንድ ነጥብ ሰባት ሚሊየን ቶን የነበረው የሀገሪቱ ሲሚንቶ የማምረት አቅም ፥ አሁን 11 ነጥብ 5 ሚሊየን ቶን የደረሰ ሲሆን ፥ ይህም ስድስት ሚሊየን ቶን ከሆነው ዓመታዊው የሀገር ውስጥ ፍጆታ በእጅጉ የላቀ መሆኑን የባልደረባችን ባሃሩ ይድነቃቸው ዘገባ ያመለክታል ።
Source:-Fana broadcasting corporate
- 696 reads